የደመና ጽላሎት በተራራዎች አናት ላይ እንደሰፈፍ ጥግ ከሚያረብብበት ከዚያ ምድር የተፈጥሮን ጥልቅ ሚስጥር ለማስተዋል ለተፈቀደላቸዉ ለእነሱ ልዩ መገለጥ አለዉ፡፡ የሀገራችን የጋራና የሸንተረር እንዲሁም የጠፍ ምድር ጉዞ ይህን እንድንታዘብ ከበረከቱ ያቋድሰናል፡፡ ፈጣሪ እንዝርቱን እያሾረ፣የጉም ባዘቶ እየፈተለ ለተራራ ያለዉን ፍቅር ለመግለፅ ሲል ባሻዉ ሰዓት ነጭ ጋቢ ማልበስ ስራዉ መሆኑን መመልከት የሚሻ ኮንታ ይገኝ! • ከኮንታ ሰማይ ስር ያለሰዉ ልጆች መጠበብ ተፈጥሮ በራሱ አይነኬ ኃይሉን ዕዉን እያደረገ የተፈጥሮን ዉብ ሚስጥር መግለጽ የየዕለት መክሊቱ ሲሆን ይታያል፡፡ •
“የኔን ነገር ትቼ የሰዉን ነገር ሳድን እንደ ከሳ ቀረ ጎኔ ሳይደነድን” እንዲል የሀገሬ ገጣሚ የራሳችንን ፀጋ ጠገብ የምድር ስጦታዎች በእኛዉ በራሳችን ፊት የተነሱ መሆናቸዉ ከአስተዉሎታችን ሸሽተዉ ከምናባችን ሊርቁ ግድ ሆኗል፡፡ • የኮንታ ህዝብ ከእናት ምድሩ ያለ ስስት ካጋተዉ ምንጮቹ እየተጎነጨ በአራዊቶቿ እስትንፋስ ጎጆዎቹን እያሞቀ በተፈጥሮ ችሮታ የተሞላ የምድር በረከቷን እየተቋደሰ ከወጣ ገባ ሸንተረርና የጫካ ደኗ ሳይኳረፍ በክብር ለዘመናት ኖረዋል፡፡ • አስደሳች መልክዓ ምድር አረንጓዴ ፀጋና በረከት የተቸረ ምድር መወደስ አይበዛበትም፡፡ • ኢትዮጵያዊነት ድንበር የለዉም፤የአንዳችን ታሪክና ገድል ለአንዳችን የዉበት ካባ የሚደርብበት ምን ጊዜም ቢሆን ከተናጠል ድል በላይ በጋራ ድላችን ላይ የምንደምቅበት ሲሆን ይታያል፡፡ ይህ ልንኖርለት የሚገባ እዉነት በጋራ እሳቤና በጋራ ኢትዮጵያዊነት እየደመቀ መጓዝ መቀጠሉ አይቀርም፡፡ • ኮንታ የበርካታ አስደናቂ ትዕይንቶች መገኛ ምድር ናት፡፡ ከእነዚሁ አስደናቂ እዉነቶች ዉስጥ ሀይማኖታዊ ገድል የሚተረክባቸዉ፣ ድንቅ ተዓምራት የሚፈፀምባቸዉ፣ጥንታዊ ዐቢያተ ክርስቲያናት ባለቤት መሆኗ ጎልቶ ይስተዋላል፡፡ ከእነዚህ ጥንታዊ አቢያተ ክርስቲያናት ለአብነት በ1882 ዓ.ም የተመሰረተዉ የገንጂ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን፣ የአጋሬ ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያንና የአመያ ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን ተጠቃሽ ናቸዉ፡፡
• ከ130 ዓመታት በላይ ዕድሜ ያስቆጠሩ ጥንታዊ አብያተ ክርስቲያናት በዘመን ሽግግር ዉስጥ የራሳቸዉን ተዓምራዊ ክስተት ዕዉን እያደረጉ ዛሬም ድረስ ለአካባቢዉ ህዝብ ስርዓተ እምነት መፈፀሚያ ሆነዉ ያገለግላሉ፡፡ እነኚህ ጥንታዊ አቢያተ ክርስቲያናት ዕድሜ ጠገብና የጥብቅ ደን ባለቤት መሆናቸዉ ልዩ ግርማ ሞገስ አላብሷቸዋል፡፡ • የተፈጥሮ ልዩ ተዓምራዊ ሚስጥራት የሚገለጡበት የኮንታ ዞን አዉሮፓዊያን የተለያዩ ሚስጥራትን ከእናት ምድር ኢትዮጵያ በሚበረብሩበት በዚያ ወቅት አሜሪካዊያን፣ እስራኤላዊያን፣ ሩሲያዊያን፣ እንግሊዛዊያን፣ ጀርመናዊያን፣ ጣሊያናዊያንና ሌሎች ዜጎች የኮንታን ምድር ተመላልሰዉበታል፡ • ከኮንታ ሰማይ ስር ያደፈጡ እዉነቶች ልዩ ናቸዉና አንዱን ጉዳይ አንስተን ሌላኛዉን ጉዳይ ማለፍ አይቻለንም፡፡ • በኮንታ ሰማይ ስር እምነት፣ኃይማኖታዊ ድርሳኑን ይገልጣል፤ታሪክ ያለፈ ገድሉን ይዘክራል፤ተፈጥሮ ኃያልነቱን ምስል እየከሰተ ያሳያል። ኮንታ የእነዚህ ድምር ውጤት ውህድ ሆና ሌላኛውን የኢትዮጲያዊነት ገጽ እንዲህ ትገልጣለች። • በኮንታ ምድር ከሚገኙ ታሪካዊ መስህቦች ውስጥ ሾኬላ ዋሻና ፏፏቴ አንዱ ነው። ይህ ዋሻ “ሾኬላ” የሚለውን ስያሜ ያገኘው ከዋሻው አናት ላይ እየተወረወረ ከሚወርደው ፏፏቴ ስም እንደሆነ ይነገራል። ፏፏቴው እያዤ የሚያወርደው ውሃ ነጠብጣብ ያለው ሲሆን ይኸው ነጠብጣብም የራሱ ቅርጽ እየያዘ ወደ ድንጋይነት የሚቀየርበት ትዕይንት ልዩ ሆኖ ያስደምማል።
• በርካታ የተፈጥሮ ሀብቶች ያሏት ኮንታ ስሟን ደጋግመን እንድንጠራ ከሚያደርጉ ስጦታዎች አንዱ የጨበራ ጩርጩራ ብሄራዊ ፓርክ ነው። በጨበራ ጩርጩራ ብሄራዊ ፓርክ ውስጥ የጎሽም ሆነ የዝሆን መንጋ በርቀት አሻግሮ ማየት ይቻላል። አልያም በስካውት አጉሊ መነጽር በመታገዝ በቅርብ ርቀት ያለውን ሁኔታ መከታተል እንጂ የዱር እንስሳትን ቀርቦ መመልከት አይቻልም። ከፓርኩ አካባቢ ሳይርቁ በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎች ቤተሰብ መስርተው፣ዘርተውና አምርተው ያለፍርሃት ቤት ሰርተው ሲኖሩ ይታያል። እራስን ከጎሽ፣ ከዝሆን፣ አንበሳና ነብር ጋር ተቀራርቦ መኖር ከባድ ቢሆንም ኮንታዎች ጋ ግን ቀላል ሆኖ በምድራዊ እውነት ሲተገበር ይታያል። • የኮንታዎች ከአራዊት ጋር ተስማምቶ የመኖር ጥበብ እንዲህ ከታየ ለኮንታዎች እንዲህ ቢባልላቸው አይከፋም። “እኔስ በሀገሬ እንኳን ሰው ወፍ አለምዳለሁ” ከሚለው ሀገራዊ ብሂል ይልቅ “እኔስ በሀገሬ እንኳን ሰው ጎሽ አለምዳለሁ” ቢባልላቸው አያንስባቸውም። • የኮንታ ህዝብና ምድር ሰዋዊ መልካምነትን ተሻግሮ አራዊቶችን አላምዶና አብሮ በመኖር ታሪኩ ውስጥ ማንነቱን አስመስክሯል።


