ህንግጫ
የኮንታ ብሔር በርካታ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ ባህላዊ፣ ታሪካዊ እና ተፈጥሯዊ ቅርሶች ባለቤት መሆኑ ይታወቃል፡፡ ከእነዚህ ዉስጥ አንዱ የዘመን መለወጫ ወይም የሕንግጫ በዓል ነዉ፡፡ ስለ ዘመን መለወጫዉ ከማዉራታችን በፊት በህዝቡ ዘንድ የሚነሱ ሶስት የተለያዩ ትርጓሜዎች ሲሰጡ ቆይተዋል፤ እነሱም ሙጬ፣ ቶኪቤአ እና ሕንግጫ ሲሆኑ ከህዝቡም ዉስጥ አንዳንዶቹ ዘመን መለወጫን ሙጬ (Muuc’e) ሌሎቹ ደግሞ ቶኪ ቤአ (Tooki-Be’a) አብዛኛዉ የሕብረተሰብ ክፍል ህንግጫ ( Hingic’aa ) በማለት የየራሳቸዉን ትርጉም እየሰጡ ባህላዊ ይዘቱን ሳይለቅ በዓሉን እያከበሩ ቆይተዋል፡፡ ነገር ግን ህንግጫ ባህላዊ ይዘቱ እንደተጠበቀ ሆኖ የትርጉም አሰጣጡ ቀደምት አባቶች ሲያከብሩ የሰጡት ስያሜና ትዉፊት በተግባር ባለመዋሉ የጋራ የሆነ ስያሜ ሳይሰጠዉ ቢቆይም ‹‹ሙጬ ›› ማለት ከጳጉሜ 1 እስከ ጳጉሜ 5/6 ድረስ ያሉ ቀናትን የሚያመላክት ሲሆን በእነዚህ ቀናት ዉስጥ በተለይም ጤፍ ቢዘራ የማይበቅልና ቢበቅልም እንኳን ከግንዱ ተቆርጦ የሚወድቅ እንዲሁም ሳያድግ ቀጭጮ ይቀራል ተብሎ ስለሚታመን ወቅቱ ‹‹ ሙጬ ›› ተብሏል፡፡
‹‹ ቶኪ ቤአ ›› ማለት ደግሞ ወደ አዲስ ዓመት መሸጋገሪያ ማለትም “ትርኳሽ” በሚወጣበት ቀን የቤተሰብ አባላት በሙሉ ጠግበዉ ካላደሩ ‹‹ቶኪ ቤአ›› የሚባል መንፈስ በዕለቱ መዝኖ በማየት ዓመቱን በሙሉ እንደተራበና እንደቀለለ ይከርማል ተብሎ ስለሚታመን ያንን ለማመልከት የተጠቀሙት ቃል ስለሆነ የዘመን መለወጫ አንዱ ክዋኔ ነዉ፡፡ በመሆኑም ‹‹ ሕንግጫ ›› የሚለዉ የብሔሩ የዘመን መለወጫ በዓል እንደሆነ የዕድሜ ባለፀጋዎችና የተለያዩ የታሪክ መጽሐፍቶች ይመሰክራሉ፡፡ የኮንታ ሕዝብ የዘመን መለወጫ በዓል ማክበር የጀመረዉ በኦሞ፣ በጎጀብ እና በዝግና ተፋሰስ መኖር ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ በዓሉን ሲያከብሩ እንደ ነበረ ይነገራል፡፡ ሆኖም በዓሉ መቼና እንዴት ተጀምሮ እያደገ እንደመጣ ትክክለኛውን ጊዜ የሚጠቁም የጽሑፍ መረጃ ባይኖርም ለበዓሉ ታሪካዊ አመጣጥ የራሱ አመልካች መረጃዎች እንዳሉ ከቀደምት አባቶች በአፈ-ታሪክ እና አንዳንድ የጽ ሑፍ መረጃዎች ያረጋግጣሉ፡፡ ይህም በኮንታ መንግሥት ተመስርቶ ግዛቱን ተቆጣጥሮ መኖር ከጀመረበት ጊዜ ጀምሮ ማለትም የመጀመሪያው የአራ ዘረ-ግንድ ቀዳሚ ንጉስ “ካቲ ኤማዶ” ዘመነ መንግስት በ12ኛዉ መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ ይበልጥ በተጠናከረ ሁኔታ በቤተሰብ ደረጃም ሆነ ከጎረቤት ጋር በጋራ በመሆን በዓሉን እያከበሩ ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ መሆኑ በታሪክ ይነገራል፡፡ የህንግጫ በዓል ታሪካዊ ዳራ ባህልና ታሪክ ባህልና ታሪክ የህንግጫ በዓል አከባበር በኮንታ ! የህንግጫ በዓል አከባበር በኮንታ ! የበዓሉ አከባበርና ዕሴት ‹‹ህንግጫ›› ማለት እንደ ብሔሩ አባቶችና የታሪክ ምሁራን አገላለጽ የሁለት ቃላት የ‹‹ሂን›› እና የ‹‹ጊጫ›› ዉህድ ነዉ፡፡
‹‹ሂን›› ማለት ወደዚያ አስፋ/ፊ ሲሆን ‹‹ጊጫ›› ማለት አሳምር፣ ጥረግ፣ አጽዳ፣ ፋቅ (Giid’ara) የሚል ትርጉም ይሰጣል፡፡ በመሆኑም ከዕለቱ በዓል ጋር የሚያያዝበት ምክንያት ጎረቤት በዓሉን አብሮ ለመታደም፤ወጣቶች በበዓሉ ወቅት ለጭፈራ እና ለምርቃት ሲመጡ ባማረና ጽዱ በሆነ አካባቢ እንዲያከብሩ እንዲሁም በዓሉ ሲከበር እንግዳ ለመቀበል ለመመራረቅ ከየጎረቤቱ አዲስ ዓመትን ለማክበር እና አዲሱ ዓመት ከጨለማ ወደ ብርሃን፣ ከርሃብ ወደ ጥጋብ ሲሸጋገሩ ብሩህ ተስፋን ሰንቀዉ በእርቅና በጥጋብ ለምድሪቱ ሠላምን፣ በረከትን፣ ፍቅርን፣ ጤንነትን፣ በመመኘት የሚቦርቁበት አካባቢ መሆኑን ያሳያል፡፡ አዲስ ዓመት የብሩህ ተስፋ አመልካች በመሆኑ ያንን ለማመልከት የተጠቀሙት ቃል ሲሆን ከበዓሉ ዝግጅት ጋር ይያያዛል፤ይኸዉም ደጃፍን አስፍተህ/ሽ አጽዳ/ጅ /kariya/ Aassade Giic’c’aa፣ ተብሎ ይገለጻል፡፡ ለበዓሉ ከሚዘጋጅ የምግብ ዓይነቶች ዉስጥ አንዱ አንጮቴ ወይም Ushshushi ya Giic’c’aa እና በበዓሉ ተዉቦና ደምቆ ለመታየት እንሶስላ ወይም wusoluwa Giic’aa ከሚለዉ ጋርም የተያያዘ ነዉ፡፡
የኮንታ ብሔር የራሱ የሆነ የዘመን አቆጣጠር ያለዉ ሲሆን የዘመን አቆጣጠሩ የመጀመሪያ የመስቀል ወር / Mask’ala Aginaa / ይባላል፡፡ በህንግጫ በዓል አከባበር ወቅት ወጣቶች ከሚጫወቱት ጨዋታ “Hoyabee salo, wod’aassaa wosikkee , andoli bole, wohee baabo baabo, koole kooli godaa” ተጠቃሾች ናቸዉ፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ የህንግጫ በዓል እስከሚደርስ ድረስ ከቤተሰብ ጀምሮ እስከ ጎረቤት የተጣላ ሳይታረቅ ወደ አዲሱ ዓመት መሸጋገር ስለሌለበት የተጣሉ ግለሰቦች በጎረቤት ሽማግሌ ይቅር ለእግዚአብሔር ይባባላሉ፡፡ ከቤት ርቆ ያለም ሆነ ከቤት ዉጭ ያለ ማንኛዉም የቤተሰብ አባል ወደቤት ሳይገባ ትርኳሽ ወይም “Ts’iifaa” ስለማይወጣና ዉጭ ከቀረ በዚያዉ ይቀራል ተብሎ ስለሚታሰብ የግድ ወደቤት ከገባ በኋላ ትርኳሽ ወይም “Ts’iifaa” በመያዝ “እርኩስ መንፈስ ዉጣ” እያለ ከዚህ በታች በተገለጸዉ መልክ ይፈፀማል፡፡ የትርኳሹን እጄታ በመያዝ እና በማወዛወዝ ወደ ዉጪ የሚያወጣዉ አባወራ ለአዲሱ ዓመት ያደረሰዉን ፈጣሪ እያመሰገነና መጪዉ ዘመን የደስታ፣ የፍቅር፣ የጤንነት፣ የሠላም፣ የአንድነትና የጥጋብ እንዲሆን እየተማፀነ እቤት ዉስጥ ያለዉ የአሮጌዉ ዘመን ክፉ መንፈስ እንዲወጣ እያንዳንዱን የቤት ዉስጥ ቁሣቁስ ለአብነት መኝታዉን፣ መከታዉን፣ ምሰሶዉን፣ ወጋግራዉን፣ የከብቶችን በረት፣ ( ከበሬ ጫንቃ ከላሞች ግት) መዉጫ በሩን በትርኳሹ እየነካ ‹‹የረሃብ የበሽታ የጥላቻ ክፉ መንፈስ ከዚህ ቤት ዉጣ›› እያለ ካዳረሰ በኋላ ትርኳሹን ከቤት አዉጥቶ ወደ ዉጪ አርቆ ይወረዉራል፡፡
ትርኳሹ (Ts’iifaa) በሚወጣበት ቀን በዕለቱ ለእራት የሚዘጋጅ ምግብ ማብሰያዉን ሞልቶ ይዘጋጃል፤እንዲሁም በቤት ዉስጥ ያሉ የምግብም ሆነ የዉሃና የወተት ዕቃዎች በምግብ፣ በዉሃና በወተት ተሞልተዉ እና ተከድነዉ ማደር አለባቸዉ፤ምክንያቱም እነኝህ ቁሳቁሶች ጎደሎ ሆነዉ የሚያድሩ ከሆነ ዓመቱን በሙሉ ችጋርና ርሃብ ከቤት አይወጣም ተብሎ ይታመናል፡፡ የዘመን መለወጫ በዓል ማብሰሪያ በአካባቢዉ ታዋቂ ወይም የዕድሜ ባለፀጋ በሆኑ አባቶች ቤት በመጀመሪያዉ ቀን በጋራ ይከበራል፤ በበዓሉ አከባበር ቀን የሚወጣዉ ትርኳሽ በችቦ መልክ ሣይሆን በምድጃ ዉስጥ እየነደደ ካለዉ የማገዶ ጉማጅ ከነፍሙ ተመዞ በመያዝ ይወጣል፡፡ የዚህ ጉማጅ ስም በአካባቢዉ አጠራር “ፂፋ” ይባላል፡፡ ከዚያም በኋላ የቤተሰቡ አባላት እና ጥሪ የተደረገላቸዉ ጎረቤቶች እንደየ ዕድሜአቸዉ ቦታ ቦታቸዉን ከያዙ በኋላ የዕድሜ ባለፀጋ የሆኑ ከ1-3 በሚደርሱ ሽማግሌዎች ምርቃት ይደረጋል፡፡ ምርቃቱም ፡ የተለያዩ ባህላዊ ምግቦች ቀርበዉ “ቦርዴ” በትልቅ እንስራ አሙልቶ በማፍሰስ በሴቶች እልልታ ታጅቦ ጠላዉን ለእያንዳንዱ ታዳሚ በማዳረስ በሚከተለዉ መልኩ የምረቃ ሥነ ሥርዓት ይከናወናል፡፡
ከተሞላዉ እንስራ በዋንጫ የተቀዳ ጠላ በመጀመሪያ የተሰጣቸዉ የዕድሜ ባለፀጋዎች እና መራቂዎች በሚከተለዉ መልክ ይመርቃሉ፡ • ‘በአሮጌዉ ዓመት ሲያጣላንና ሲያጋጨን የነበረዉ ክፉ መንፈስ ከመሃላችን ፈጣሪ ያርቅልን’ ! • ‘ይህ ጠላ ሞልቶ እንደፈሰሰ ሁሉ ጤንነት፣ ፍቅር፣ ሠላምና ጥጋብ በሃገራችን፣ በአካባቢያችንና በሰፈራችን እንዲሁም በእያንዳችን ቤት እንዲዚህ ሞልቶ ይፍሰስ’ ! • ‘አዲሱ ዓመት የሕዝቡ እና የመንግስት አንደበት የሚጣጣምበት ዘርተን የምንቅምበት፣ ወልደን የምንስምበት፣ ነግደን የምናተርፍበት፣ ከቤት የወጣዉ በሰላም የሚመለስበት፣ ያፈራነዉን በሰላምና በፍቅር የምንበላበት ዘመን ያደርግልን’ ! • ‘በአዲሱ ዓመት ስትወጡ እንቅፋት አይምታችሁ፤ ስትናገሩ እዉነተኛ ሃሳብ አይጥፋባችሁ፤ ፍቅራችን እንደ ሰማይ ጉም እንደ ምድር ሰርዶ እንደ ጉንዳን ሕብረትና አንድነት እግዚአብሔር ያድለን ! በመጨረሻም ከእኛ የተረፈዉን እግዚአብሔር ይመርቃችሁ’ ! በማለት ያጠቃልላሉ፡፡

